…
ስሜነህ
የማህፀን በር ካንሰርን ከአገር ብሎም ከአፍሪካ ለማጥፋት ብዙ ስራዎች እየተሰሩ ይገኛሉ።
“የማህፀን በር፣ የጡት እና የፕሮስቴት ካንሰርን ከአፍሪካ እናጥፋ” ጉባኤ ከፊታችን ሐምሌ 17 እስከ 20 ቀን 2008 ዓ.ም
“የአስር ዓመታት ስኬቶቻችንና ትሩፋቶቻችን” በሚል መሪ ሀሳብ ይካሄዳል። ይህንኑ ጉባኤ መሰረት በማድረግም ስለማህጸን ካንሰር አንዳንድ
መረጃዎች መለዋወጥ የዘመቻው አንድ አካል ነውና ወጋችንም እርሱው ይሆናል።
የማህፀን በር ካንሰር መንስኤው ሂማንፓፒለማ የተባለ ቫይረስ ነው። በዚህ ቫይረስ
ምክንያት የተከሰተ ኢንፌክሽን በሰውነት ውስጥ ለረጅም ጊዜ በሚቆይበት ጊዜ የማህፀን በር ካንሰር እንደሚከሰት በዘርፉ ምርምር ያደረጉ
ልሂቃን ይገልጻሉ። ይህ ቫይረስ በሰውነት ውስጥ ከገባ በኋላ የቅድመ ካንሰር ምልክቶች ማሳየት የሚጀምረው በአማካይ ከ10 እስከ
15 ዓመታት ባሉት ጊዜያት ውስጥ ነው። ይህ ማለት ደግሞ አንዲት ሴት በ15 ዓመቷ የግብረ-ስጋ ግንኙነት ማድረግ ብትጀምር እና
ቫይረሱ ሰውነቷ ውስጥ ቢገባ እንኳን እነዚህን የቅድመ ካንሰር ምልክቶች እስከ 30 እና 35 ዓመቷ ድረስ ላታሳይ ትችላለች ማለት
ስለሚሆን ጉዳቱን ያከብደዋል። እነዚህ የቅድመ ካንሰር ምልክቶች በማህፀን በር ሊይ ከተስተዋሉ በኋላም ወደ ካንሰርነት ለመለወጥ
ከ10 እስከ 15 ዓመታት የሚፈጅበት መሆኑን ነው ጠበብቱ በምርምራቸው ያረጋገጡት። ከዚህ እድሜ ጀምሮ ግን ወይም ወደ ካንሰር ከተለወጠ
በኋሏ ቫይረሱ በማህፀን የውስጥ ክፍልች ላይ ለውጥ ያመጣል። የማህፀንን ግድግዳ በመበከል ቁስለት ይፈጥራል።እንደጠበብቱ መረጃ ቁስለቱ
ከማህፀን ግድግዳ አልፎ በደም ውስጥ በመግባት መላ ሰውነትን ያዳርሳል።
የማህፀን በር ካንሰር ዋነኛ ቫይረስ በግብረስጋ ግንኙነት የሚተላለፍ ሲሆን፣ ሰባ
ከመቶ በላይ የሚሆኑት ታማሚዎችም የቫይረሱ ተሸካሚዎች ናቸው። በተጨማሪም በግልፅ የማይታወቁ መንስኤዎች እንደሚኖሩም ባለሙያዎቹ
ይገልጻሉ። ለማህፀን በር ካንሰር አጋላጭ የሆኑ በርካታ ነገሮችም አሉ ከእነዚህም የመጀመሪያው፤ ሴቷ የመጀመሪያ የግብረ ስጋ ግንኙነት
የጀመረችበት የእድሜ ክልል እንደሆነ ያወሳሉ። አንዲት ሴት የግብረ ስጋ ግንኙነት የጀመረችው በአስራዎቹ የእድሜ ክልል ውስጥ ከሆነ
ለማህፀን በር ካንሰር የመጋለጥ እድሏ ከፍተኛ ይሆናል። ለአባላዘር በሽታዎች አልያም ለኤች አይ ቪ/ ኤዴስ የተጋለጠች ከሆነች እንዲሁም
ከአንድ በላይ የወሲብ ጓደኛ ካላት አሊያም ከአንድ በላይ የወሲብ ጓደኛ ያለው ጓደኛ ካላት ለዚሁ የካንሰር አይነት የመጋለጥ እድሏ
ይጨምራል። የሰውነት በሽታን የመከላከል አቅም የሚቀንሱ መድሃኒቶችን የሚወስዱ ሰዎችም ለማህፀን በር ካንሰር የመጋለጥ እድላቸው
ከፍተኛ ነው ሲሉ ባለሙያዎቹ ያስጠነቅቃሉ።
ለማህፀን
በር ካንሰር አጋላጭ የሆኑት ነገሮች በአብዛኛው ከዝቅተኛ ኢኮኖሚ እና የአኗኗር ዘይቤ ጋር የተያያዙ ስለመሆናቸውም ልሂቃኑ ሳይጠቅሱ
አያልፉም። በለጋ እድሜ ጋብቻ በመመስረት ግብረ-ስጋ ግንኙነት መጀመር፣ ልጆችን በላይ በላዩ መውለድ
ለዚህ በሽታ አጋላጭ ከሚባል የአኗኗር ዘይቤ ጋር የተያያዙ ጉዳዮች ናቸው። የማህፀን በር ካንሰር ከበለፀጉት
አገራት ይልቅ በማደግ ላይ ባሉት አገራት ላይ ስርጭቱ ከፍተኛ የሚሆነውም ስለዚህ ነው። ከዚህ ውጪ ደግሞ
ሲጋራ የሚያጨሱ ሴቶች ከሌሎቹ በበለጠ ለማህፀን በር ካንሰር ያላቸው ተጋላጭነት
ከፍተኛ ነው። የማህፀን በር ካንሰር ሊካለከሉት የሚቻል በሽታ ሆኖ ሳለ መከላከል የማይቻለውም
ከላይ ከተመለከተው ዝቅተኛ የአኗኗር ሁኔታ ጋር በተያያዘ ነው። ሴቶች ለጤናቸው ቅድሚያ በመስጠት በየጊዜው
የቅድመ ካንሰር ምርመራ ስለማያደርጉ ለዚህ
በሽታ የመጋለጥ እድላቸው ይጨምራል።
ሌላውና ከዚሁ ዝቅተኛ ኢኮኖሚ ጋር የሚያያዘው ጉዳይ፤ የማህፀን በር ህክምና በሚፈለገው
መጠን አለመስፋፋቱ ነው። ኅብረተሰቡ ስለበሽታው ግንዛቤ ኖሮት መታከም ቢፈልግ እንኳን የህክምና አገልግሎቱ
ሰፊ እና በሁሉም ቦታ የሚሰጥ ባለመሆኑ በሽታውን ለመከላከል
ከባድ ያደርገዋል።
የማህፀን በር ካንሰር በሽታው ሲጀመር ምንም አይነት ምልክት አያሳይም። ቫይረሱ በሰውነት
ውስጥ ገብቶ ምልክቶች ለማሳየት በርካታ ዓመታት ስለሚፈጅበትም ምልክቶቹን በቶሎ መገንዘብ አይቻልም። ነገር ግን
ህክምና ሳያገኝ ሲቆይና ቫይረሱ በሰውነት ውስጥ የሚኖረው ስርጭት እየበዛና እየሰፋ ሲሄድ ምልክቶቹ መታየት ይጀምራሉ። ምልክቶቹ
መታየት የሚጀምሩትም በሽታው ከቅድመ ካንሰርነት ወደ ካንሰርነት
በሚሸጋገርበት ወቅት ነው። ምልክቶቹንም ባለሙያዎቹ የቅድመ ካንሰር እና የካንሰር ብለው ይከፍሏቸዋል። ነገር ግን፤ በቅድመ የማህፀን በር ካንሰር ወቅት ብዙም ምልክቶች
አይታዩም። በአጠቃላይ ስንመለከተው ግን የማህፀን በር ካንሰር መኖሩን ከሚጠቁሙት ምልክቶች
መካከል ህመም አልባ የሆነ ደም
ከማህፀን መውጣት የመጀመሪያው ነው። ይህ ክስተት የሚከሰተውም መደበኛ ባልሆኑ ጊዜያት ነው። እነዚህ ጊዜያትም
ከመደበኛ የወር አበባ ጊዜ ውጪ፣ ከግብረ ስጋ ግንኙነት በኋላ፣ ከማረጥ በኋላ፣ ብልትን ከታጠቡ በኋላ ሊሆን
ይችላል። ከዚህ በተጨማሪም የሚታየው ምልክት መጥፎ ጠረን ያለው እና ውሃማ ቀለም
ያለው የማህፀን ፈሳሽ መውጣት፣ የጎን፣ የወገብ እና የእግር ህመም ስሜት መሰማት፣ የሽንት ቧንቧ
ወይም የፊንጢጣ መድማት፣ የእግር እብጠት፣ እንዲሁም የሽንት ወይም የሰገራ ማምለጥ (fistula) ዋና ዋናዎቹ ናቸው።
የማህፀን በር ካንሰርን አስቀድሞ በሚደረግ
ጥንቃቄ እና ምርመራ መከላከል የሚቻል መሆኑንም ከላይ ስለተመለከቱት መንስኤዎችና ምልክቶች አስረጅ የሆኑን ምርምሮች ይገልጻሉ።
የበሽታው መንስኤ የሆኑትን ነገሮች በማስወገድ ለበሽታው ያለውን
ተጋላጭነት መቀነስ ይቻላል። ባልታወቀ ምክንያት የሚመጣውን ለመከላከል ደግሞ ቅድመ ካንሰር ምርመራ በማድረግ
ሁኔታውን ማወቅ ይቻላል። ዋና ዋና የመከላከያ መንገዶቹም፤ ሂውማን ፓፒልማ ቫይረስ የሚተላለፈው በግብረ ስጋ ግንኙነት ስለሆነ
ለዚህ ቫይረስ በማያጋልጥ መልኩ ጥንቃቄ የተሞላበት የወሲብ ግንኙነት ማድረግ ያስፈልጋል ። ነገር ግን ይሄንን
ቫይረስ ኮንዶም በመጠቀም መከላከል የማይቻል እንደሆነ ጠበብቱ ያሰምራሉ። ሁለተኛው
ሊወሰድ የሚገባው ጥንቃቄ ደግሞ፤ ሲጋራ የሚያጨሱ ሴቶች ሲጋራ ማጨሳቸውን ወዲያው ማቆም
ይኖርባቸዋል። ዋናውና የበሽታው መከላከያ ግን ቅድመ ካንሰር ምርመራ በተገቢው ጊዜ ማድረግ ነው። ለቅድመ
ካንሰር ምርመራ የሚደረጉት ምርመራዎች ሁለት አይነት ናቸው። የመጀመሪያው ቪ አይ ኤ የሚባለው
ምርመራ ነው። ይህ ምርመራ በሴቷ ማህፀን ላይ ኬሚካል በመቀባት እና ለአምስት ደቂቃ
ያህል በማቆየት የሚሰራ ምርመራ ነው። በዚህ የቆይታ ጊዜ ውስጥ በሚታየው ለውጥም ካንሰር መኖር አለመኖሩን
ማረጋገጥ ይቻላል። ይኸኛው ምርመራ በአጭር ጊዜ ውስጥ የሚሰራና ውጤቱም በዓይን በማየት ብቻ ለማወቅ የሚቻል ነው። በዚህ የምርመራ
ዘዴ የተመረመሩ ሴቶች በየሦስት ዓመቱ ተመሳሳይ ምርመራ እንዲያደርጉ ይመከራል። ሁለተኛው
የቅድመ ካንሰር ምርመራ ፓፕ ስሚር የሚባለው ዓይነት ነው። በዚህኛው የምርመራ ዘዴ ከማህፀን ላይ የፈሳሽ
ናሙና በመውሰድ ምርመራ ይደረጋል።ይህ የምርመራ ዓይነት ከበድ የሚል እና ረዘም ያለ ጊዜም
የሚወስድ ነው። ይሄንን አይነቱን ምርመራ ማድረግ የሚቻለውም በተወሰኑ የህክምና ማዕከላት ነው። በዚህ ዓይነቱ መንገድ
የተመረመረች ሴት የካንሰር ቫይረስ በሰውነቷ ውስጥ አለመኖሩ ከተረጋገጠ በኋላ በየአምስት ዓመቱ ምርመራ እንድታርግ
ይመከራል።
የቅድመ ካንሰር ምርመራ በማድረግ የማህፀን በር ካንሰር ከመከሰቱ ከአስር ዓመት በፊት አስቀድሞ ማወቅ ይቻላል። የቅድመ ካንሰር መርመራ እድሜያቸው ከ21 ዓመት በላይ የሆኑ የግብረስጋ
ግንኙነት
ለጀመሩ እና ከኤች
አይ
ቪ
ቫይረስ
ጋር
ለሚኖሩ
ሴቶች መሰጠት
ይኖርበታል።
ምርመራው
በዚህ
መልኩ
በመቀጠል
እድሜያቸው
ከ65
ዓመት
በላይ
ሲሆን፣
አልያም
ለተከታታይ
ሦስት
ምርመራዎች
የተመዘገበው
ውጤት
ነፃ
ከሆነ
ምርመራውን
ማቆም
እንደሚቻል ተመራማሪዎቹ ይገልጻሉ። እናም ይህንን ገዳይ የሆነ በሽታ እንደዋዛ ማየት ተገቢ አይሆንም።
No comments:
Post a Comment